ህዳር 5 ቀን 2015 ዓ.ም.፡- ከሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር በመተባበር ሌሎችን ለመርዳት ሮጣለሁ አመታዊው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የድጋፍ ማሰባሰብ ዘመቻ ዘንድሮ 1 ሚሊዮን ብር ለማሰባሰብ አቅዶ እየሰራ እንደነበር ይታወቃል፡፡
በየአመቱ እንደሚያደርገውም የተመረጡትን አክሽን ፎር ዴቨሎመንት (በድርቅ የተፈናቀሉ ወገኖች ላይ የሚሰራ)፤ ኢማጅን ዋን ደይ (ህፃናት ላይ የሚሰራ) እና ምዥዥጓ ሎካ የሴቶች ማጎልበቻ ማህበር ተጠቃሚዎች ያደርጋል፡፡
በዘንድሮው የገቢ ማሰባሰብ ስራ ላይ ተሳታፊዎች በተለይም የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሰራተኞች የውድድሩን ቲሸርት በተጨማሪ ዋጋ በመግዛት የግል አስተዋፅኦ ያደረጉ ሲሆን ከዚህም በተጨማሪ በተለያዩ ሃገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ለዚሁ ዘመቻ ገንዘብ በማሰባሰብ የራሳቸውን ጉልህ ድርሻ ወስደዋል፡፡
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ “ሌሎችን ለመርዳት ሮጣለሁ” በሚል መርህ በየዓመቱ ከሩጫው ጋር በተያያዘ በሚያከናውነው የበጎ አድራጎት ሥራ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል፡፡ ባለፉት አስራ ሰባት አመታት ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ ሰብስቦ የተለያዩ ድርጅቶችን ሲያግዝ መቆየቱም ይታወቃል፡፡
የ2015 ሶፊ ማልት ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አለም አቀፍ 10ኪ.ሜ. ውድድር የፊታችን ህዳር 11 ቀን 2015 ከጠዋቱ 1፡10 ጀምሮ ከ41ሺህ ተሳታፊዎች ጋር የሚካሄድ ይሆናል፡፡ በውድድሩ ላይ 500 የሚደርሱ አትሌቶች እና 35 የአካል ጉዳተኛ ተወዳዳሪዎች ይሳተፋሉ፡፡
ለበለጠ መረጃ በ0911601710 ወይም hilina@ethiopianrun.org ሕሊና ንጉሴ ብለው ይጠይቁ፡፡