ህዳር 5 ቀን2014 የሚካሄደው 2014 ቶታልኢነርጂስ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የምዝገባ ፕሮግራሙን ዛሬ በይፋ አስጀመረ፡፡ ምዝገባ ሰኞ ሃምሌ 12 ቀን ጠዋት 2 ሰአት ላይ ይከፈታል፡፡ ተሳፊዎች ምዝገባ ኦንላይን በተቀመጠው የቴሌግራም ቦት(@greatethiopianrunbot) ማድረግ ሲኖርባቸው የመመዝገቢያ ክፍያም የክፍያ አጋር በሆነው አሞሌ ብቻ ይሆናል፡፡
ከምዝገባ መክፈቻ ፕሮግራሙ ጋር ተያይዞም፣ በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነውን የ3ኪ.ሜ. በቀን የእግር ጉዞ ዘመቻ የትራንስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ዳግማዊት ሞገስ በተገኙበት ተገልጧል፡፡ ይህ የ#3ኪ.ሜ. በቀን የእግር ጉዞ ፕሮግራም ሰዎች በእለት ተእለት ህይወታቸው በስራ መግቢያ እና መውጫ ሰዓት ላይ ለትራንስፖርት ከመሰለፍ አመቺ የሆኑ መንገዶች ባሉበት ቦታ የተወሰነውን የመንገዳቸው አካል ቢራመዱ ከጤናም፤ ሰዓት ከመቆጠብም፤ ከትራንስፖርት መጨናነቅም ከተማችንንም ህዝቡንም ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ታሳቢ ሆኖ የተዘጋጀ ዘመቻ መሆኑ ተገልጧል፡፡ ይህን ዘመቻ ለማስጀመር እና ለማስለመድ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከትራንስፖርት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የሚያከናውነው ይሆናል፡፡
የ2014 ቶታልኢነርጂስ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ መልዕክት በአገር አቀፍ ደረጃ በዘመቻ መልክ እየተካሄደ ያለው ፅዱ- በየሜዳው አይፀዳዱ፤ በመፀዳጃ ቤት ይጠቀሙ! ሲሆን ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ይህን መልእክት ከዩኒሴፍ ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር አቅርቦታል፡፡ ዩኒሴፍ ኢትዮጵያ በከተማም ሆነ በገጠራማው የኢትዮጵያ ክፍል በንፁህ፤ ተደራሽና ዘላቂ የሆነ የውሃ አቅርቦት አንዲሁም የተሟላ የንፅህና አጠባበቅን ለህፃናትና ለቤተሰቦቻቸው በማድረስ ስራ ላይ ተሰማርቶ የሚሰራ አለም አቀፍ ድርጅት ነው፡፡
ከ1950 ጀምሮ ስራ የጀመረው በአፍሪካ ትልቁ የፔትሮሊየም አምራች ኩባንያ ቶታል ኢትዮጵያ፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ከ150 በላይ አገልግሎት ሰጪ ቅርንጫፎች ያሉት ሲሆን ከዚህም ስራው በተጨማሪ የተለያዩ የማህበረሰባዊ ጉዳዮች ላይ ተሳትፎ በማድረግ የሚታወቅ ነው፡፡
የ2014 ቶታልኢነርጂስ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በአጋርነት አብረውት ከሚሰሩት መካከል የኢትዮጵያ አየር መንገድ፤ ሶፊማልት፤ አሞሌ፤ ቱሪዝም ኢትዮጵያ፤ ኢንዶሚ፤ ሳስ ፋርማሲቲካልስ፤ ሃያት ሬጀንሲ እና አርኪ ውሃ ዋነኞቹ ናቸው፡፡
25000 ተሳታፊዎችን የሚያስተናግደው የዘንድሮ ሩጫ መመዝገቢያ ዋጋ 590 ብር መሆኑ ታውቋል፡፡
ስለ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ
– የ2014 ቶታልኢነርጂስ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ 10ኪ.ሜ. 21ኛው ዙር ነው፡፡ የመጀመሪያ ዙር ውድድር ህዳር 16 ቀን 1994 ተካሂዷል፡፡
– ቶታል ኢትዮጵያ በ1995 እና 1996 የስያሜ ስፖንሰር የነበረ ሲሆን በድጋሚ ከ2008 ዓ.ም. ጀምሮ የስያሜ ስፖንሰርነቱን በድጋሚ ወስዶታል፡፡
– የ20ኛው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከታቀደለት የመሮጫ ቀን በ8 ሳምንታት ዘግይቶ ጥር 2 ቀን 2013 ዓ.ም. በ12500 ተሳታፊ ብቻ ተካሄዷል፡፡
– ከ1998 ዓ.ም. ጀምሮ ከ15,000,000 ብር በላይ በሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ ፕሮግራሙ ለመሰብሰብ ችሏል፡፡