ጋዜጣዊ መግለጫ
የ2014 ቶታልኢነርጂስ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ለመካሄድ 6 ሳምንታት ብቻ ቀሩት
መፀዳዳት በሽንት ቤት የዘንድሮው ውድድር መልዕክት ነው
መስከረም 21 ቀን 2014 ዓ.ም.፡- አለም አቀፍ ዋና ዋና የማራቶን ውድድሮች በብዛት በሚካሄድበት ሰሞን የሚደረገው እና ህዳር 5 የሚካሄደው የ2014 ቶታልኢነርጂስ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ለመካሄድ 6 ሳምንታት ብቻ ቀርተውታል፡፡
ታላቁ ሩጫ በየአመቱ እንደሚያደርገው በዘንድሮ ውድድር ላይ ከዩኒሴፍ ጋር በመተባበር አካባቢን ከብክለት ነፃ የሆነ እና ለህፃናት ተስማሚ እንዲሆን የሚያበረታታውን – መፀዳዳት በሽንት ቤት- የሚል የውድድር መልዕክት ያስተላልፋል፡፡መፀዳጃ ቤትን እንደ አንድ ወሳኝ የቤት አካል አድርገው በመቁጠርና በአግባቡ ገንብቶ በመጠቀም እራስንና ቤተሰብን ከተላላፊ በሽታዎች መጠበቅ እንደሚቻል የሚመክረው ዩኒሴፍ፡ የጋራ መፀዳጃ ቤቶችን በአግባቡ መጠቀም እና ማፅዳትም እራስን ፣ ቤተሰብን እና በአካባቢ ያሉ ነዋሪዎችን ከተላላፊ በሽታዎች ለመጠበቅ እንደሚረዳ ማስገንዘብን በተለያዩ መንገዶች እየሰራበት ይገኛል።
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በየአመቱ የተለያዩ ማህበራዊ መልዕክቶችን ከማንሳትም በተጨማሪ ለተለያዩ ማህበራት የገንዘብ እርዳታ አሰባስቦ ይሰጣል፡፡ ዘንድሮም “የወጣቶች አትሌቲክስ ፕሮጀክት“ እና “ግሬስ ለልጆችና ቤተሰቦቻቸው ማዕከል“ እርዳታ ለማድረግ አቅዷል፡፡
የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የኦፕሬሽን ሀላፊ አቶ ዳግም ተሾመ “ሩጫውን ሲወዳደሩ እርዳታ ለሚያሻቸው ህፃናት፣ ሴቶች እና አረጋውያን መታሰቢያነት አድርጎ መሮጥና በተጨማሪም የምንችለውን ማድረግ ደስታ ይሰጣል፡፡ ታላቁ ሩጫ ላለፉት አመታት ከ19 ሚሊዮን ብር በላይ ሰብስቦ የተለያዩ ድርጅቶችን ረድቷል ከነዚህ ውስጥ ተጠቃሹ በዋግህ ምራ ዞን ያሰራው ትምህርት ቤት ተጠቃሽ ነው:: የቲሸርቱ ዋጋም 900 ብር ይሆናል” ብለዋል፡፡
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ለዘንድሮው ሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ ዘመቻ ይሆን ዘንድ የተወሰኑ የመሮጫ ቲሸርቶችን በተጨማሪ ዋጋ ለመሸጥ ያዘጋጀ ሲሆን ክፍያውን በአሞሌ በማድረግ ከዛሬ ጀምሮ መግዛት የሚቻል እንደሆነም አሳውቋል፡፡ ኦሞሌ የ2014 ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የክብር ስፖንሰር ሲሆን ለየዚህ ሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ ዘመቻም የራሱን አስተዋፅኦ እያረገ ይገኛል፡፡
የ2014 ቶታልኢነርጂስ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የያዘው አዲስ ነገር ምንድነው ?
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከፔትኮ ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ለመስራት የአባልነት ሰርተፍኬቱን ከማህበሩ በዛሬው እለት ተቀብሏል፡፡ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከፔትኮ ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በ2014 ዓ.ም. በሚያደርጋቸው ዋና ዋና ውድድሮች ላይ ለማካተት ከሚሰራባቸው ዋና ዋና ጉዳዮች ውስጥ ለመጥቀስ
- የካርቦን ልቀትን መቀነስ ላይ መስራት
- በተገኘው አጋጣሚ ሪሳይክል ማድረግን ማበረታታት
- አግባብ ያለው የቆሻሻ አወጋገድን መለማመድ
- የፕላስቲክ አጠቃቀም መቀነስን መለማመድ እና
- የወረቀት አጠቃቀም መቀነስን መለማመድ ዋነኞቹ ሲሆኑ ይህንንም ለቀጣይ ውድድሮችም የሚያስቀጥለው ይሆናል፡፡
ለበለጠ መረጃ ሕሊና ንጉሴ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ስልክ፡ 0911601710 ኢሜል፡ hilina@ethiopianrun.org