ሴቶች ብቻ የሚካፈሉበት እና በደማቅ ሁኔታ የሚደረገው አመታዊው ቅድሚያ ለሴቶች ሩጫ የፊታችን እሁድ መጋቢት 19 ቀን ይካሄዳል፡፡
የ2013 ሶፊ ማልት ቅድሚያ ለሴቶች 5ኪ.ሜ ሩጫ የኢትዮጵያ ሴቶችን ስኬት እናክብር በሚል መርህ ይካሄዳል፡፡ ለሩጫው ሁለት ቀናት በቀሩት የመጨረሻው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ይህ የሩጫ መልዕክት በአትሌቶች እና በታዋቂ የቢዝነስ ሴቶች መካከል የሚደረገው አጠር ያለ ውይይት አንዱ አካል ሲሆን፤ በዚህ ውይይት ላይም አትሌቶች በቢዝነስ አለም ላይ ያላቸውን ጥያቄዎች እንዲሁም የቢዝነስ ሴቶችም አካላዊ እንቅስቃሴን ባህል ከማድረግ አንፃር ያላቸውን ጥያቄ የሚለዋወጡ ይሆናል፡፡
ይህ የቅድሚያ ለሴቶች ሩጫ በ18 አመት ጉዞው ውስጥ ከተለያዩ የህይወት ዘርፍ፤ አኗኗር ዘይቤ ፤ እድሜ እና የትምህረት ደረጃ የመጡ ነገር ግን በራሳቸው የህይወት መንገድ አሸናፊና ጀግና የሆኑ ሴቶችን ሲያስተናግድ መቆየቱ ይታወቃል፡፡
በዚህ አመት 4 የተለያዩ የውድድር ዘርፎች የሚኖሩ ሲሆን በአትሌቶች መካከል የሚካሄደው ውድድር 150 አትሌቶችን የሚያሳትፍና አንደኛ የሚወጣው የ50000 ብር ተሸላሚ የሚሆንበት ሲሆን፤ የሶፊ አካል ብቃት መፈተኛ ፉክክር ደግሞ ሁለተኛው እና ተወዳዳሪዎች የተሻለ የሩጫ ሰዓት ያስመዘግቡበታል ተብሎ የሚጠበቀው ውድድር ይሆናል፡፡ በዚህ አመት የተጨመረው አዲሱ የወጣት ተፅእኖ ፈጣሪ አሸናፊዎች ውድድር ደግሞ ለውድድሩ የተለየ ቀለም ከመጨመሩም በላይ ወጣቶች በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ ያላቸውን ተፅእኖ የሚያሳይ ይሆናል፡፡ በየአመቱ የሚደረገው የቲ-ሸርት ዲዛይን ፉክክርም የፈጠራ ችሎታ ያላቸውን ተሳታፊዎች ተሸላሚ የሚያደርግ ይሆናል፡፡
ተሳታፊችን እና የተለያዩ ሩጫው ላይ ተሳታፊ የሚሆኑ ወገኖችን ከኮቪድ ለመከላከል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ቅድመ ሁኔታዎች ያጠናቀቀ ሲሆን ተሳታፊዎች ወደ ውድድር ቦታው ሲፈርሱ የሙቀት መለኪያ እንዲሁም ሳኒታይዘር ይደረግላቸዋል፤ የፊት ጭምብል ከውድድሩ መጀመር በፊት እና በኃላ ማድረግ ግዴታ ነው፤ ከዚህም በተጨማሪ ተሳታፊዎች በሚቆሙበት ጊዜ እንዳይቀራረቡ በተሰመረላቸው ቦታ ላይ የሚቆሙ ይሆናል፡፡ ውድድሩ በ3 የተለያዩ ማእበሎች የሚካሄድ ሲሆን እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች እንዲሳኩ ተግተው የሚሰሩ የበጎ ፈቃደኞች በየቦታቸው በመሆን የሚያግዙ መሆኑም ታውቋል፡፡
የዘንድሮው ውድድር አትላስ ሆቴል አካባቢ መነሻ እና መድረሻውን ያደርጋል፡፡ ለበለጠ መረጃ hilina@ethiopianrun.org ወይም 0911601710