ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ሃ/የተ/የግል ማህበር የ2014 ቶታልኢነርጂስ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል 10ኪ.ሜ ውድድር ህዳር 5 ሲካሄድ ከአረንጓዴ ሩጫ ጋር በተያያዘ የተለያዩ አዳዲስ አሰራሮችን ለመጀመር ማቀዱን አስታውቋል፡፡
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከፔትኮ ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በ2014 ዓ.ም. በሚያደርጋቸው ዋና ዋና ውድድሮች ላይ የሚደረጉ የአካባቢ ማፅዳት እና ሪሳይክል የሚደረጉ ግብአቶችን ለውድድር ቀን ለመጠቀም ቅድመ ሁኔታውን አጠናቋል፡፡
ይህ የአረንጓዴ ሩጫ ዘመቻ በውስጡ ከሚይዛቸው ይዘቶች ውስጥ
· የካርቦን ልቀትን መቀነስ ላይ መስራት
· በተገኘው አጋጣሚ ሪሳይክል ማድረግን ማበረታታት
· አግባብ ያለው የቆሻሻ አወጋገድን መለማመድ
· የፕላስቲክ አጠቃቀም መቀነስን መለማመድ እና
· የወረቀት አጠቃቀም መቀነስን መለማመድ ዋነኞቹ ሲሆኑ ይህንንም ለቀጣይ ውድድሮችም የሚያስቀጥለው ይሆናል፡፡
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ሃይልን በአለም አቀፍ ደረጃ ለገበያ እያቀረበ ያለው እንዲሁም ዘይት፤ የተፈጥሮ ነዳጅ አረንጓዴ ጋዝ እና የመብራት ሃይል በማቅረብ የአካባቢ ብክለትን በመከላከል ለሰዎች የለት ተለት ኑሮ አስፈላጊ የሆኑ ግብአቶችን ከሚያቀርበውና በአዲስ መልክ ከተዋቀረው የውድድሩ የስያሜ ስፖንሰር ቶታልኢነርጂስ ጋር መስራቱም የዚህን የአረንጓዴ ውድድር ዘመቻ የሚያበረታታ የሚያደርገው ሲሆን ከቶታልኢነርጂስ በተጨማሪም ከዩኒሴፍ ጋር በመተባበር አካባቢን ከብክለት ነፃ የሆነ እና ለህፃናት ተስማሚ እንዲሆን የሚያበረታታውን – መፀዳዳት በሽንት ቤት- የሚል የውድድር መልዕክት ያስተላልፋል፡፡
የዚህን የአረንጓዴ ሩጫ ዘመቻ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጰያ ለመጀመር ምን እንዳነሳሳው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ስራ አስኪያጅ ዳግማዊት አማረ ሲገልፁ ‘ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በየአመቱ በሚያደርጋቸው ውድድሮች ላይ የማህበራዊ ጉዳዮችን ማንሳቱ የተለመደ ሲሆን፤ የጉዳዩ አስፈላጊነት በየጊዜው እየጨመረ ከመምጣቱ አንፃር ስለ አረንጓዴ ሩጫ እና ተያያዥ ጉዳዮች አሁን ማንሳቱ ተገቢ ነው ብለዋል፤ አያይዘውም ተሳታፊዎች እና የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅባቸውን ሃላፊነት እንደሚወጡም ተስፋ እናደርጋለን’ ብለዋል፡፡
ከአረንጓዴ ሩጫው ጋር በተያያዘ ታላቁ ሩጫ ከአስጀመራቸው ስራዎች ውስጥ ከወረቀት ነፃ የሆነው የምዝገባ ስርአት ከአሞሌ ጋር በመተባበር መዘርጋት፤ የትራንስፖርት ሚኒስቴር እና ሃይሌ ገብረስላሴ በጋራ ያስጀመሩት የ#3ኪሜ በቀን ዘመቻን ማድረግ ከካርቦን ልቀት ጋር በተያያዘ ከሚመጣ አየር ብክለት መከላከል ከተጀመሩ ስራዎች ውስጥ ተጠቃሽ ናቸው፡፡
ለበለጠ መረጃ የፊታችን አርብ መስከረም 21 ቀን በሃያት ሬጀንሲ ከጠዋቱ 4፡30 በምናደርገው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የምናሳውቅ ይሆናል፡፡