ሩጫን በምክንያት መሮጥ- ‘ሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ’ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ፕሮግራም
ሃሙስ ታህሣሥ 11 – ለ18ተኛ ጊዜ ከተካሄደው ቶታል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ጋር ተያይዞ ለ6ተኛ ጊዜ የተካሄደው ሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ ፕሮግራም በዚህኛውም አመት በተወሰኑ የታላቁ ሩጫ ተሳታፊዎች እና ድርጅቶች በጎ ፈቃደኝነት ከታቀደለት 1.7 ሚሊዮን ብር አስበልጦ 1.8 ሚሊዮን ብር ለማሰባሰብ ችሏል፡፡
እንደወትሮው 4 የተለያዩ እርዳታ የሚያስፈልጋቸውን ሃገር በቀል የእርዳታ ድርጅቶች ማለትም የኢትዮጵያ ስኳር ህመም ማህበር፤ የአዲስ አበባ ሴቶች ማህበር፤ ጆይፉል ላይፍ እንዲሁም ስለ እናት ማህበርን መርጦ የተሰባሰበውን ገንዘብ በዛሬው እለት አስረክቧል፡፡ እያንዳንዳቸው የ450ሺ ብር እርዳታ ያገኙ ሲሆን ድርጅቶቹም በህጻናት፤ በሴቶችና በተለያዩ የእድሜ ክልል ላይ ያሉ ሰዎችን የሚያገለግሉ ስራዎችን በመስራት ላይ እንዳሉም ታውቋል፡፡
ታላቁ ሩጫ በቀጣይም የሃዋሳ ሃይቅን እንንከባከብ በሚል መሪ ቃል የ2011 ታል ሃዋሳ ግማሽ ማራቶንን የካቲት 3 ቀን በሃዋሳ ከተማ እንደሚያካሂድ የታወቀ ሲሆን ለ21 ኪ.ሜ. እንዲሁም ለ7 ኪ.ሜ. እና ለህፃናት ተሳታፊዎች ምዝገባ በታላቁ ሩጫ በኢትጵያ ቢሮ መጀመሩንም አስታውቀዋል፡፡
ሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ ፕሮግራም
ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በየአመቱ ከሚያከናውናቸው ፕሮግራሞች ውስጥ በተለይም ከአለም አቀፉ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ጋር አያይዞ የሚያከናውነው ሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ ፕሮግራም አንዱ ነው፡፡ ሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ ላለፉት 6 አመታት ያለማቋረጥ የተከናወነ ሲሆን የዘንድሮውን ጨምሮ ከ28 በላይ ድርጅቶችንም ተጠቃሚ አድርጓል፡፡ በየአመቱ የተለያዩ ተደራሽነት የሚያስፈልጋቸውን በጎ አድራጎት ላይ የተሰማሩ ድርጅቶችን ተጠቃሚ የሚያደርገው ይህ ፕሮግራም ከአመት አመት የሚያሰባስበውን ገንዘብ መጠን በመጨመር 1.8 ሚሊዮን ብር ማሰባሰብ ላይ ደርሷል፡፡ በአጠቃላይ ባለፉት 6 አመታት 10 ሚልዮን ብር ተሰብስቦ ለሚመለከተው ወገን ተረክቧል፡፡ ለቀጣይ አመታትም ይህን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡
ለበለጠ መረጃ ሕሊና ንጉሴ 0911601710 ኢሜል – hilina@ethiopianrun.org